· ‘‘Ashkot’’/መሐላ
- infoforal
- Mar 9, 2022
- 1 min read
‘‘Ashkot’’ ወይም መሐላ የአንድ ነገር እውነትነት ማረጋገጫ ቃል ነው፡፡ የድራሼ ማህበረሰብ እሴት የሆነው Ashkot/መሐላ የአንድን ነገር ስለመፈጸምም ሆነ ላለመፈጸም ማስረገጫ ነው፡፡ ስለሆነም ማህበረሰቡ በዋናነት በሦስት እሳቤ አካላት ይምላሉ፤ በእህት/ወንድም፣ በጎሣ እና በንጉሥ ስም፡፡ ወንዶች ‘Alawtawo’ ይላሉ (እህቴን እንደ ማለት ነው) ወይም የመጀመሪያ እህቱ ስም ጠርቶ ይምላሉ፤ ሴቶች ‘Alawawo’ ይላሉ (ወንድሜን እንደ ማለት ነው) ወይም የመጀመሪያ ወንድሙ ስም ጠርቶ ይምላሉ፡፡ ወንድም ወይም እህት የለላቸው ደግሞ ወላጆች በመጀመሪያ ልጃቸው ስም (አባት ሴት ልጁን፤ እናት ወንድ ልጇን)፣ ወንድ ልጅ ያባቱን እህት ስም (በአክስቱ) ሴት ልጅ ደግሞ በአባቷ ስም ይምላሉ፡፡ አንዳንድ ጊዜ ባልተለመደ ሁኔታ የመማያ ወንድም ወይም እህት እያለች (ከጥላቻ፣ ቅራኔ ምክንያት) ለልጃቸው ካላቸው ጥልቅ ፍቅር የተነሳ በልጃቸው ስም የሚምሉ አሉ፡፡ አሊያም ሁለቱም ፆታ በጎሣቸው ስም ይምላሉ፡፡ ለምሳሌ ጎሣቸው ‘Aelayt’ የሆኑት ሰዎች ‘Aelaya’ ይላሉ፡፡ በሦስተኛ ደረጃ የድራሼ ማኅበረሰብ በጊዜው መሪ በሆነው ንጉሥ ስም ይምላል፡፡
በእንዲህ ዓይነት የድራሼ ህብረተሰብ የአንድን ነገር እውነትነት ጥግ ለማስረገጥ በወንድሙ/እህቱ ስም ወይም በጎሣው ስም አሊያም በመጨረሻ ደረጃ የመሪው ንጉሡን ስም በመጥራት መሐላ ያደርጋል፡፡ ማህበረሰቡ ራሱን የሚያውቀው ጥቂት የሚናገር ቁጥብ፣ ጨዋ፣ ከውሸት የራቀ፣ የሰውን የማይነካ፣ ባህሉን የሚያከብር፣ ባጠቃላይ ‘Etant’ በሚባል እሴት ህልውና አብሮ ይኖራል፡፡ ከዚህ እሳቤ ተቃራኒ ያልተረጋገጠ መረጃ የሚያወሩ፣ ችኩል ችኩል የሚሉ፣ እውነት ላልሆነ ነገር የሚምሉ፣ ብዙ የሚናገሩ፣ የሰውን የሚፈልጉ፣ የባህል እሴትን አልፎ የሚታዩትን ‘Hawudha’ ብሎ ይጠራቸዋል፡፡
በዚህ መሠረት የአብዛኛው ማህበረሰብ ክፍል ‘Etant’ ሆኖ ጥቂት ክፍሉ ግን ‘Hawudha’ መሆኑን ህብረተሰቡ ስለሚያውቁት የማን መሐላ እውነት እንደሆነ ይታወቃል፡፡ በተደጋጋሚ የሚምሉትን ይገስጻቸዋል፤ ከአታላይነታቸው ተግባር እንዲመለሱ ይመክራቸዋል፡፡ የመሐላው እውነትነት በፍሬው ስለሚታወቅም የአብዛኛው መሐላ በማህበረሰብ ዘንድ ተቀባይነት ያለው ቢሆንም አሁን ላይ ይህ መልካም እሴት በአንዳንድ ሁኔታዎች በመሸረሸር ላይ ይገኛል፡፡
Comments